የማህፀን ጫፍ ቅድመ ካንሰር ምርመራ ዘመቻ ተጀመረ

በእንጅባራ ዩኒቨርሲቲ ለሁለተኛ ዙር የተካሄደው የማህፀን ጫፍ ቅድመ ካንሰር የግንዛቤ ፈጠራ እና የምርመራ ዘመቻ ተጀምሯል፡፡

የእንጅባራ ዩኒቨርሲቲ የህክምና እና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ የተከታታይ ሙያ ማጎልበቻ ማዕከል(CPD)አስተባባሪ ወ/ሮ የውብምርት ሻረው(ረዳት ፕሮፊሰር) ከነሐሴ 21/2016 ዓ.ም ጀምሮ ለሁለተኛ ዙር የማህፀን ጫፍ ቅድመ ካንሰር የግንዛቤ ፈጠራ ሲሰጥ መቆየቱን ጠቅሰው ከእንጅባራ ጠቅላላ ሆስፒታል ጋር በመተባበር የምርመራ ዘመቻ መጀመሩን ገልጸዋል፡፡ አክለውም የማህፀን ጫፍ ካንሰር ከሌሎች ካንሰሮች በተለየ ትኩረት የተሰጠው በስርጭቱ ሁለተኛ ስለሆነ ብቻ ሳይሆን ከሌሎች ካንሰሮች በተለዮ ያልዘገየ አግባብነት ያለው ምርመራ እና ህክምና ከተደረገ 98% መከላከል እና መዳን ሚችል በመሆኑ ነው፡፡
የአለም የጤና ድርጅት በ2024 ሪፖርት እንደሚያሳየው ለማህጸን ጫፍ ካንሰር 99% ምክንያቱ Human papilloma virus (HPV) ነው። አብዛኛው HPV ኢንፊክሽን ምልክቶች አያሳይም፡ ለዛም ብዙዎቹ ህክምና ፈልገው የሚመጡት በመጨረሻው ደረጃ ነው።
በመጨረሻው ደረጃ ደግሞ ህክምናውን በቅርብ ለማግኘት አስቸጋሪ እና ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቅ ከመሆኑ በተጨማሪም የመዳን እድሉም በጣም ያነሰ ነው።
(CPD) ምክረ ጤና ግሩፕ ከህዝብ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ሥራ አስፈጻሚ ጋር በመሆን 500 በራሪ ወረቀቶችን አዘጋጅቶ የግንዛቤ ፈጠራ ሲሰራ ቆይቶ የምርመራ ዘመቻው መጀመሩን ተናግረዋል።
ስለሆነም ዩኒቨርሲቲው ያዘጋጀው የምርመራ ዘመቻ በእንጅባራ ጠቅላላ ሆስፒታል እየተሰጠ ሲሆን ሁሉም ሴቶች ሄደው ምርመራውን በነጻ ማድረግ እንደሚችሉ ገልጸዋል፡፡

መስከረም 8/2017 ዓ.ም፤

እንጅባራ ዩኒበርሲቲ