በአማራ ክልል የሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ፎረም በዚገም ወረዳ ለሚገኙ ተፈናቃዬች የምግብ ድጋፍ አደረገ

በአማራ ክልል የሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ፎረም በአዊ ብሄረሰብ አስተዳዳር ዚገም ወረዳ በጸጥታ ችግር ምክንያት ለተፈናቀሉ ወገኖች 121 ኩንታል በቆሎ የምግብ ድጋፍ አድርጓል፡፡

የፎረሙ ዋና ጸሐፊ ታፈረ መላኩ(ዶ/ር) በአማራ ክልል ባሉ ዩኒቨርሲቲዎች የተቋቋመው ፎረም የማህበረሰቡን ችግር ከመፍታት አንጻር የጋራ ጥናትና ምርምር ከማድረግ ባሻገር በክልሉ በተለያዩ ጊዜያት በሰው ሰራሽ እና ተፈጥሯዊ አደጋዎች ምክንያት ለሚከሰቱ ችግሮች ምላሽ በመስጠት የተለያዩ ሰብዓዊ ድጋፎችን ሲያደርግ መቆየቱን ገልጸዋል፡፡ የዚህ አካል የሆነው በአዊ ብሄረሰብ አስተዳደር ዚገም ወረዳ በጸጥታ ችግር ምክንያት ለተፈናቀሉ ወገኞች የ400 ሺህ ብር በቆሎ ድጋፍ የተደረገ ሲሆን በተመሳሳይ በቅርቡ በሰሜን ጎንደር ዞን በመሬት መንሸራተት ምክንያት ጉዳት ለደረሰባቸው የማህበረሰብ ክፍሎች የማሽላ ምግብ ድጋፍ መደረጉን ተናግረዋል፡፡ ድጋፉን የተረከቡ የወረዳ አስተባባሪዎች ችግር ላይ ለሚገኙ ወገኞች በአጭር ጊዜ ውስጥ በማዳረስ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡም አሳስበዋል።
የእንጅባራ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንትጋርዳቸው ወርቁ (ዶ/ር) ዩኒቨርሲቲው ቀደም ሲል ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገበትን የቤት ክዳን ቆርቆሮ ለተፈናቃዮች ድጋፍ ማድረጉን አስታውሰው፣ እንጅባራ ዩኒቨርሲቲ አባል የሆነበት በአማራ ክልል የሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ፎርም ለተፈናቃዬች 400,000 ብር የሚወጣ የበቆሎ ድጋፍ በማድረጉ ለፎረሙ እና ለአባል ዩኒቨርስቲዎች ምስጋና አቅርበዋል።