በእንጅባራ ዩኒቨርሲቲ በአፕል ችግኝ ልማት ዙሪያ ስልጠና መሰጠት ተጀመረ

በእንጅባራ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ውስጥ በግብርና፣ ምግብና ዓየር ንብረት ኮሌጅ አማካኝነት ለዩኒቨርሲቲው አትክልተኞች በአፕል ልማት ዙሪያ የንድፈ ሀሳብና የተግባር ስልጠና መሰጠት ተጀምሯል።

በዩኒቨርሲቲው ሆርቲካልቸር መምህርና የስልጠናው አስተባባሪ የሆኑት አቶ አዲሱ ሙሉቀን በግቢው ውስጥ ከ3ሺ በላይ የደጋ አፕል ችግኞች መተከላቸውን አስታውሰው ችግኞችን ለሚንከባከቡ አትክልተኞች ስለ አፕል አመራረት ዝርያና መረጣ፣ ቅጥያ ማስወገድን፣ መገረዝና በሽታ መከላከልን፣ ቀለበት የመስራትን ጠቀሜታ፣ የጉዝጓዝ አደራረግን በተጨማሪም የአፈር አሲዳማነትን ለመከላከል የኮንፖስት አዘገጃጀትና አጠቃቀም ዙሪያ በተግባር የታገዘ ስልጠና እየተሰጠ ይገኛል ብለዋል፡፡

በስልጠናው ያገኘናቸው አቶ አጋሉ ሙሉ እና ወ/ሮ ስመኝ አያሌው ከዚህ በፊት በልምድ ይሠሩ እንደነበር አስታውሰው የአፕል ችግኝ አኮታኮትና ኮምፖስት አጨማመር እንዲሁም በእንክብካቤ ወቅት መደረግ ያለበትን ጥንቃቄ በስልጠናው ግንዛቤ እያገኙ መሆናቸውን ተናግረዋል። ስልጠናው ለተከታታይ ሶስት ቀናት የሚቀጥል መሆኑም ተገልጿል።

መስከረም 8/2017 ዓ.ም፤

እንጅባራ ዩኒቨርሲቲ